+++
ብዙውን ጊዜ አጋንንት የሚገለጹበት አሠራር በሚያስፈራ መልክ ነው:: ንግግራቸው በትዕቢት የተሞላ ነው::
/ኢሳ.10:14/ በአብዛኛው ራሳቸውን እየለወጡ የማስመሰል ሥራ ይሠራሉ:: ባሕታውያን ሲተኙ ለጸሎት እየቀሰቀሱ
እንቅልፍ ይነሣሉ; አንዳንዴም ለጾም ያደሉ በማስመሰል ምንም እንዳንመገብ ይመክሩናል:: ለጸሎት በሚተጋ መነኩሴ
አምሳል ይገለጣሉ:: ይህንን ሁሉ የሚያደርጉት ሰዎች ለጊዜው ከአቅም በላይ በመትጋት በሗላ ግን እንዲሰለቹና
ተዳክመው ተስፋ እንዲቆርጡ የብሕትውና ኑሮ ሸክም የበዛበትና የማይቻል ነው በሚል ሃሳብ እንዲያቁዋርጡት ለማድረግ
ነው:: አጋንንት የማስመሰልና የማስፈራራት ሥራ የሚያበዙት በእውነት የሚያሸንፉበትን
ኃይላቸውን ስላጡና ዲያብሎስ በጌታችን የማዳን ሥራ ስለ ወደቀ ነው:: በተጨማሪም አጋንንት ትንቢት መናገር የሚችሉ
ወይም ሃሳባችንን ሳንገልጸው በፊት ማወቅ የሚቻላቸው መስለው ይቀርባሉ:: ለምሳሌ አንድ ወንድም ወደኛ ለመምጣት
አስቦ መንገድ ሲጀምር አጋንንት መንፈስ ስለሆኑ ቀድመው ይደርሱና 'እከሌ ይመጣል' ብለው ይናገራሉ:: እኛም ሰውየው
ሲመጣ በእውነት ትንቢት የተነገረ ስለ ሚመስለን እንደነቃለን:: በዚህ ዘዴ አጋንንት የማጭበርበር ሥራ ይሠራሉ
እንጂ ከቶ ትንቢት መናገር ወይም የሰውየውን ሃሳብ ማወቅ አይችሉም::[የበረሓው ኮከብ- ቅዱስ እንጦንስ; ዘደረሰ
ቅዱስ አትናቴዎስ]
No comments:
Post a Comment